×
ፈልግ
ስለህይወት እና ስለእግዚአብሄር በነፃነት
 ጥያቄ የሚጠይቁበት ድረገጽ

ከእግዚአብሔር ጋር መጀመር

ክርስቶስ በሕይወትህ እንዳለ እርግጠኛ መሆን ትችላለህ

አስቀድመን ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን ወደ ሕይወትህ እንዲገባ መጋበዝህን ስለነገርከን ለእኛ መልካም ዜና ስለሆነ በጣም መደሰታችንን ለንገልጽልህ እንወዳለን። ይህንን ውሳኔ ወስነህ ጌታ ኢየሱስን ወደ ልብህ ስትጋብዘው ፣ እግዚአብሔር በእርግጥም ይህንን ጥያቄህን መቀበሉንና አለመቀበሉን ለማረጋገጥ በእርግጥ እግዚአብሔር አምላክ ሰምቶኛል ? ብለህ መጠየቅህ ትክክል ነው። የእኛም መልስ አዎ ሰምቶሃል ነው። በ1ኛ ዮሐ. 5፥14-15 ላይ እንዲህ ተጽፏል። « በእርሱ ዘንድ ያለን ድፍረት ይህ ነው፤ እንደፈቃዱ አንዳች ብንለምን ይሰማናል። የምንለምነውንም ሁሉ እንዲሰማልን ብናውቅ ከእርሱ የለመንነውን ልመና እንደተቀበልን እናውቃለን። » ስለዚህ ወደ ሕይወታችን እንዲገባ ጌታ ኢየሱስን ብንጠይቀው አስቀድሞ ተስፋ ሰጥቶናልና ወደ ሕይወታችን ይገባል።

በራዕይ 3፥20 ላይ ጌታ ኢየሱስ አንዲህ ብሎ ተስፋ ሰጥቶናል። «እነሆ በደጅ ቆሜ አንኳኳለሁ ፤ ማንም ድምጼን ቢሰማ ደጁንም ቢከፍትልኝ ፥ ወደርሱ እገባለሁ፤ ከእርሱም ጋር እራት እበላለሁ ፣ እርሱም ከእኔ ጋር ይበላል። » የልብህን በር ለእግዞአብሔር አምላክ ከፍተህለታል? ከፍተህለት ከሆነ ፣ ምን የሚያደርግ ይመስልሃል ? ወደስህተት የሚመራህ ይመስልሃል?

ክርስቶስን የተቀበሉ ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዳላቸው መጽሐፍ ቅዱስ ያረጋግጣል

‹‹ እግዚአብሔርም የዘላለምን ሕይወት እንደሰጠን ይህም ሕይወት በልጁ እንዳለ ምስክሩ ይህ ነው። ልጁ ያለው ሕይወት አለው የእግዚአብሔር ልጅ የሌለው ሕይወት የለውም። የዘላለም ሕይወት እንዳላችሁ ታውቁ ዘንድ በእግዚአብሔር ልጅ ስም ለምታምኑ ይህን ጽፌላችኃለሁ›› (1ዩሐ.5፡11-13)

- ክርስቶስ በአንተ ሕይወት ውስጥ ስላለና እስከ መጨረሻ ስለማይተውህ እግዚአብሔርን አመስግነው (ዕብ 13፡5) ።

- ከዚህ በኃላ የተለየ ስሜት ባይሰማህስ?

በስሜቶችህ ላይ አትደገፍ

ልንታመን የሚገባን እግዚአብሔር በቃሉ በሰጠን ተስፋ እንጂ በስሜቶቻችን አይደለም። ክርስቲያን የሚኖረው በእግዚአብሔርና በቃሉ ላይ በእምነት በመደገፍ ነው። ቀጥሎ ያለው የባቡር ምሳሌያዊ ስዕል የሚያሳየው፡-

- እውነት ማለትም እግዚአብሔርና ቃሉ

- እምነት ማለት በእግዚአብሔርና በቃሉ ላይ ያለን መደገፍ

- ስሜት ደግሞ የእምነታችንና የመታዘዛችን ውጤት ሊሆን እንደሚገባ ነው።

- ባቡሩ ሊንቀሳቀስ የሚችለው በሞተሩ ነው እንጂ በተጎታቹ አይደለም። በዚሁ መንገድ ልንታመን የሚገባን በእግዚአብሔር ታማኝነትና በተስፋ ቃሉ ላይ ነው። የእምነት ነዳጅ በእግዚአብሔር ቃል እውነት ላይ በተጨመረ መጠን በህይወትህ የእርሱ ኃይል አብልጦ ይገለጣል። እምነትህ በስሜትህ ላይ እንዲደገፍ አትፍቀድለት። ‹‹ በእምነት እንጂ በማየት አንመላለስምና›› (2ቆሮ 5፡7)

ከእግዚአብሔር ጋር ያለህን ግንኙነት ማሳደግ፡

እግዚአብሐርን በበለጠ ለማወቅ የእግዚአብሔርን ቃል መጽሐፍ ቅዱስን ለማጥናት በቂ ጊዜ ይኑርህ። በዚያም ውስጥ እግዚአብሐየር ራሱን በይበልጥ እንዲገልጥልህና ግንኙነትህ እንዲያድግ በጸሎት ጠይቀው።በአዲስ ኪዳን ከወንጌላት በአራተኛው ረድፍ ላይ የሚገኘው የዮሐንስ ወንጌልን በማጥናት ብትጀምር መልካም ነው።

ቀጥሎም እግዚአብሔር አምላክን በነጻነት አነጋግረው። እኛም በፊልጵዩስ 4፥6-7 ያለውን ክፍል በሕይወትህ ይፈጸም ዘንድ እናደፋፍርሃለን ፤ እንደዚህ ይላል።- «በነገር ሁሉ በጸሎትና በምልጃ ከምሥጋና ጋር በእግዚአብሔር ዘንድ ልመናችሁን አስታውቁ እንጂ በአንዳች አትጨነቁ። አዕምሮን የሚያልፍ የእግዚአብሔር ሰላም ልባችሁንና አሳባቸሁን በክርስቶስ ኢየሱስ ይጠብቃል። »

አሁን አንተ ክርስቶስን ተቀብለሃል

ክርስቶስን በሕይወትህ እንደ አዳኝና ጌታ እንዲሆንልህ በጋበዝከው ጊዜ ብዙ ነገሮች በሕይወትህ ተከናውነዋል። ከእነዚህም ዋና ዋናዎቹ

  1. ክርስቶስ ወደ ሕወትህ መጥቷል (ራዕ 3›20)
  2. ኃጢያትህ ሁሉ ይቅር ተብሏል (ቆላ. 1፡14፣ 2፡ 13 )
  3. የእግዚአብሔር ልጅ ሆነሃል (ዩሐ 1፡12)
  4. የዘላለም ሕይወት አግኝተሃል (ዩሐ 5፡24 ፤ 1ዩሐ 5:11-13)
  5. እግዚአብሔር ሲፈጥርህ ያቀደልህን አዲስና እርካታ የሞላበትን ዘላለማዊ ግንኙነት ከእርሱ ጋር ጀምረሃል። (ዩሐ 10፡10፤ 2ቆሮ 5፡17)

- ክርስቶስን ከመቀበል የሚበልጥ አስደናቂ ነገር በሕይወትህ ይኖራል ብለህ ታስባለህ?

- እግዚአብሔር ለአንተ ስላደረገው ነገር አሁን በጸሎትህ ለምን አታመሰግነውም?

የቤተክርስቲያን አስፈላጊነት

ከሌሎች ክርስቲያኖች ጋር ሕብረት መፍጠር በጣም አስፈላጊ ነው (ዕብ. 10፡25፤ የሐዋ 2፡42-47)። እስከ አሁን ድረስ ቤተክርስቲያን ሄደህ የማታውቅ ከሆነ ክርስቶስ ወደሚከበርበትና ቃሉ ወደ ሚሰበክበት ስፍራ በፍቃድህ ሳታቋርጥ በመሄድ ክርስቶስን አዳኛቸው ካደረጉና ፍቅሩንም በሕይወታቸው ከሚለማመዱ ሰዎች ጋር ሕብረት ፍጠር።

የማገዶ እንጨቶች በአንድነት ሲሆኑ በድምቀት ይነዳሉ፤ ነገር ግን አንዱን እንጨት ለብቻው አውጥተን በቀዝቃዛ ስፍራ ብናስቀምጠው እሳቱ ይጠፋል። እንዲሁም አንተ የክርስትናን ሕይወት ለብቻህ መኖር ያስቸግርሃል።

ለበለጠ መረጃ፣ በዚህ አድራሻ ያግኙን።